መዝሙር 135 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

መዝሙር 135:1-21

መዝሙር 135

የምስጋና መዝሙር

135፥15-20 ተጓ ምብ – መዝ 115፥4-11

1ሃሌ ሉያ።135፥1 3 እና 21 ጭምር በአንዳንድ ትርጕሞች እግዚአብሔር ይመስገን ይላሉ።

የእግዚአብሔርን ስም ወድሱ፤

እናንት የእግዚአብሔር አገልጋዮች ሆይ፤ አመስግኑት፤

2በእግዚአብሔር ቤት፣

በአምላካችን ቤት አደባባይ የምትቆሙ አመስግኑት።

3እግዚአብሔር ቸር ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ፤

መልካም ነውና፣ ለስሙ ዘምሩ፤

4እግዚአብሔር ያዕቆብን ለራሱ፣

እስራኤልንም ውድ ንብረቱ አድርጎ መርጧልና።

5እግዚአብሔር ታላቅ እንደ ሆነ፣

ጌታችንም ከአማልክት ሁሉ እንደሚበልጥ ዐውቃለሁና።

6በሰማይና በምድር፣

በባሕርና በጥልቅ ሁሉ ውስጥ፣

እግዚአብሔር ደስ ያሰኘውን ሁሉ ያደርጋል።

7እርሱ ደመናትን ከምድር ዳርቻ ያስነሣል፤

መብረቅ ከዝናብ ጋር እንዲወርድ ያደርጋል፤

ነፋሳትንም ከማከማቻው ያወጣል።

8በኵር ሆኖ በግብፅ የተወለደውን፣

ከሰው ጀምሮ እስከ እንስሳ ቀሠፈ።

9ግብፅ ሆይ፤ በፈርዖንና በአገልጋዮቹ ሁሉ ላይ፣

በመካከልሽ ታምራትንና ድንቅን ሰደደ።

10ብዙ ሕዝቦችን መታ፤

ኀያላን ነገሥታትንም ገደለ።

11የአሞራውያንን ንጉሥ ሴዎንን፣

የባሳንን ንጉሥ ዐግን፣

የከነዓንን ነገሥታት ሁሉ ገደለ፤

12ምድራቸውንም ርስት አድርጎ፣

ለሕዝቡ ርስት እንዲሆን ለእስራኤል ሰጠ።

13እግዚአብሔር ሆይ፤ ስምህ ዘላለማዊ ነው፤

እግዚአብሔር ሆይ፤ መታሰቢያህም ከትውልድ እስከ ትውልድ ይኖራል።

14እግዚአብሔር ለሕዝቡ ይፈርዳልና፣

ለአገልጋዮቹም ይራራላቸዋል።

15የአሕዛብ ጣዖታት ከብርና ከወርቅ የተሠሩ፣

የሰው እጅ ያበጃቸው ናቸው።

16አፍ አላቸው፤ አይናገሩም፤

ዐይን አላቸው፤ አያዩም፤

17ጆሮ አላቸው፤ አይሰሙም፤

በአፋቸውም እስትንፋስ የለም።

18እነዚህን የሚያበጁ፣

የሚታመኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁኑ።

19የእስራኤል ቤት ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኩ፤

የአሮን ቤት ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኩ፤

20የሌዊ ቤት ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኩ፤

እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሆይ፤ እግዚአብሔርን ባርኩ።

21በኢየሩሳሌም የሚኖር እግዚአብሔር፣ ከጽዮን ይባረክ።

ሃሌ ሉያ።