ሶፎንያስ 1 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

ሶፎንያስ 1:1-18

1በይሁዳ ንጉሥ በአሞጽ ልጅ በኢዮስያስ ዘመን ወደ ሕዝቅያስ ልጅ፣ ወደ አማርያ ልጅ፣ ወደ ጎዶልያስ ልጅ፣ ወደ ኵሲ ልጅ ወደ ሶፎንያስ የመጣ የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው፤

ስለሚመጣው ጥፋት የተሰጠ ማስጠንቀቂያ

2“ማንኛውንም ነገር፣

ከምድር ገጽ አጠፋለሁ”

ይላል እግዚአብሔር

3“ሰውንና እንስሳን አጠፋለሁ፤

የሰማይን ወፎች፣

የባሕርንም ዓሦች አጠፋለሁ፤

ሰውን ከምድር ገጽ በማስወግድበት ጊዜ፣

ክፉዎች የፍርስራሽ1፥3 የዕብራይስጡ ቃል ትርጕም በትክክል አይታወቅም። ክምር ይሆናሉ”

ይላል እግዚአብሔር

በይሁዳ ላይ የተነገረ ጥፋት

4“እጄን በይሁዳ፣

በኢየሩሳሌምም በሚኖሩት ሁሉ ላይ አነሣለሁ፤

የበኣልን ትሩፍ፣

የጣዖታቱንና የአመንዝራ ካህናቱን ስም ሁሉ ከዚህ ስፍራ አጠፋለሁ፤

5የሰማይን ሰራዊት ለማምለክ፣

በሰገነት ላይ ወጥተው የሚሰግዱትን፣

ለእግዚአብሔር እየሰገዱ፣ በስሙም እየማሉ፣

በሚልኮምም1፥5 በዕብራይስጥ ማልካም ይባላል። ደግሞ የሚምሉትን፣

6እግዚአብሔርን ከመከተል ወደ ኋላ የሚመለሱትን፣

እግዚአብሔርን የማይፈልጉትን፣ እንዲረዳቸውም የማይጠይቁትን አጠፋለሁ።”

7በጌታ እግዚአብሔር ፊት ዝም በሉ፤

የእግዚአብሔር ቀን ቀርቧልና።

እግዚአብሔር መሥዋዕት አዘጋጅቷል፤

የጠራቸውንም ቀድሷል።

8በእግዚአብሔር የመሥዋዕት ቀን፣

መሳፍንቱንና የንጉሡን ልጆች፣

እንግዳ ልብስ የሚለብሱትን ሁሉ እቀጣለሁ።

9በዚያን ቀን፣

በመድረኩ ላይ የሚዘልሉትን ሁሉ፣

የአማልክታቸውን ቤት፣

በዐመፅና በማጭበርበር የሚሞሉትን እቀጣለሁ።

10እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

“በዚያ ቀን ‘ከዓሣ በር’ ጩኸት

በሁለተኛው አደባባይ ዋይታ፣

ከኰረብቶችም ታላቅ ሽብር ይሰማል።

11እናንት በመክቴሽ1፥11 አንዳንዶች በሞርታር ይላሉ። ገበያ የምትኖሩ ዋይ በሉ፤

ነጋዴዎቻችሁ ሁሉ ይደመሰሳሉ፤

በብር የሚነግዱትም ሁሉ ይሞታሉ።

12በዚያ ዘመን ኢየሩሳሌምን በመብራት እፈትሻለሁ፤

ተንደላቅቀው የሚኖሩትን፣

በዝቃጩ ላይ እንደ ቀረ የወይን ጠጅ የሆኑትን፣

‘ክፉም ይሁን መልካም፣

እግዚአብሔር ምንም አያደርግም’ የሚሉትን ቸልተኞች እቀጣለሁ።

13ሀብታቸው ይዘረፋል፤

ቤታቸው ይፈራርሳል፤

ቤቶች ይሠራሉ፤

ነገር ግን አይኖሩባቸውም፤

ወይን ይተክላሉ፤

ጠጁን ግን አይጠጡም።”

ታላቁ የእግዚአብሔር ቀን

14“ታላቁ የእግዚአብሔር ቀን ቅርብ ነው፤

ቅርብ ነው ፈጥኖም ይመጣል፤

በእግዚአብሔር ቀን የሚሰማው ልቅሶ መራራ ነው፤

በዚያ ጦረኛውም ምርር ብሎ ይጮኻል፤

15ያ ቀን የመዓት ቀን፣

የመከራና የጭንቀት ቀን፣

የሁከትና የጥፋት ቀን፣

የጨለማና የጭጋግ ቀን፣

የደመናና የድቅድቅ ጨለማ ቀን ይሆናል፤

16ያ ቀን በተመሸጉ ከተሞችና፣

በረዣዥም ግንቦች ላይ፣

የመለከት ድምፅና የጦርነት ጩኸት የሚሰማበት ቀን ይሆናል።

17“እንደ ዕውር እንዲራመዱ፣

በሰዎች ላይ ጭንቀት አመጣባቸዋለሁ፤

በእግዚአብሔር ላይ ኀጢአትን ሠርተዋልና።

ደማቸው እንደ ትቢያ፣

ሥጋቸውም እንደ ጕድፍ ይጣላል።

18በእግዚአብሔር የቍጣ ቀን፣

ብራቸውም ሆነ ወርቃቸው

ሊያድናቸው አይችልም።”

መላዪቱ ምድር፣

በቅናቱ ትበላለች፤

በምድር በሚኖሩ ሁሉ ላይ፣

ድንገተኛ ፍጻሜ ያመጣባቸዋልና።