መዝሙር 29 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

መዝሙር 29:1-11

መዝሙር 29

ለማዕበሉ ጌታ የቀረበ ውዳሴ

የዳዊት መዝሙር።

1እናንተ ኀያላን፣ ለእግዚአብሔር ስጡ፤

ክብርንና ብርታትን ለእግዚአብሔር ስጡ።

2ለስሙ የሚገባ ክብር ለእግዚአብሔር ስጡ፤

በቅድስናው ግርማ ለእግዚአብሔር ስገዱ።

3የእግዚአብሔር ድምፅ በውሆች ላይ ነው፤

የክብር አምላክ አንጐደጐደ፤

እግዚአብሔር በታላላቅ ውሆች ላይ አንጐደጐደ።

4የእግዚአብሔር ድምፅ ኀያል ነው፤

የእግዚአብሔር ድምፅ ግርማዊ ነው።

5የእግዚአብሔር ድምፅ ዝግባን ይሰብራል፤

እግዚአብሔር የሊባኖስን ዝግባ ይሰባብራል።

6ሊባኖስን እንደ ጥጃ፣

ስርዮንንም29፥6 አርሞንዔም የተባለው ተራራ ነው። እንደ አውራሪስ ግልገል ያዘልላል።

7የእግዚአብሔር ድምፅ

የእሳት ነበልባል ይረጫል።

8የእግዚአብሔር ድምፅ ምድረ በዳውን ያናውጣል፤

የእግዚአብሔር ድምፅ የቃዴስን ምድረ በዳ ያናውጣል።

9የእግዚአብሔር ድምፅ ወርካዎችን ይወዘውዛል፤29፥9 ወይም እግዚአብሔር አጋዘን እንድትወልድ ያደርጋል

ጫካዎችንም ይመነጥራል፤

ሁሉም በእርሱ ቤተ መቅደስ ሆኖ “ይክበር!” ይላል።

10እግዚአብሔር በጐርፍ ላይ ዙፋኑን ዘርግቶ ተቀምጧል፤29፥10 ወይም ይቀመጣል

እግዚአብሔር በንጉሥነቱ ለዘላለም በዙፋኑ ላይ ይቀመጣል።

11እግዚአብሔር ለሕዝቡ ብርታትን ይሰጣል፤

እግዚአብሔር ሕዝቡን በሰላም ይባርካል።