ምሳሌ 26 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

ምሳሌ 26:1-28

1በረዶ በበጋ፣ ዝናብ በመከር እንደማያስፈልግ ሁሉ፣

ክብርም ለተላላ አይገባውም።

2ክንፎቿን እንደምታርገበግብ ድንቢጥ ወይም ቱር እንደምትል ጨረባ፣

ከንቱ ርግማንም በማንም ላይ አይደርስም።

3ለፈረስ ዐለንጋ፣ ለአህያ መሸበቢያ፣

ለተላላ ጀርባም በትር ይገባዋል።

4ቂልን እንደ ቂልነቱ አትመልስለት፤

አለዚያ አንተም ራስህ እንደ እርሱ ትሆናለህ።

5ቂልን እንደ ቂልነቱ መልስለት፤

አለዚያ ጠቢብ የሆነ ይመስለዋል።

6በተላላ እጅ መልእክትን መላክ፣

የገዛ እግርን እንደ መቍረጥ ወይም ዐመፃን እንደ መጋት ነው።

7በቂል አንደበት የሚነገር ምሳሌ፣

ሰላላ የሽባ ሰው እግር ነው።

8ለተላላ ክብር መስጠት፣

በወንጭፍ ላይ ድንጋይ እንደ ማሰር ነው።

9በአላዋቂ አንደበት የሚነገር ምሳሌ፣

በሰካራም እጅ እንዳለ እሾኽ ነው።

10ቂልን ወይም የትኛውንም ዐላፊ አግዳሚ የሚቀጥር፣

ፍላጻውን በነሲብ እየወረወረ ወገኖቹን እንደሚያቈስል ቀስተኛ ነው።

11ውሻ ወደ ትፋቱ እንደሚመለስ ሁሉ፣

ተላላም ቂልነቱን ይደጋግማል።

12ራሱን እንደ ጠቢብ የሚቈጥረውን ሰው አይተሃልን?

ከእርሱ ይልቅ ለተላላ ተስፋ አለው።

13ሰነፍ፣ “በመንገድ ላይ አንበሳ አለ፤

አስፈሪ አንበሳ በአውራ ጐዳና ላይ ይጐማለላል” ይላል።

14መዝጊያ በማጠፊያው ላይ እንደሚዞር፣

ሰነፍም በዐልጋው ላይ ይገላበጣል።

15ሰነፍ እጁን ወጭት ውስጥ ያጠልቃል፤

ወደ አፉ ለመመለስ ግን እጅግ ይታክታል።

16በማስተዋል መልስ ከሚሰጡ ከሰባት ሰዎች ይልቅ፣

ሰነፍ ራሱን ጠቢብ አድርጎ ይቈጥራል።

17በሌሎች ጠብ ጥልቅ የሚል መንገደኛ፣

የውሻ ጆሮ እንደሚይዝ ሰው ነው።

18ትንታግ ወይም የሚገድል ፍላጻ እንደሚወረውር እብድ፣

19“ቀልዴን እኮ ነው” እያለ

ባልንጀራውን የሚያታልል ሰውም እንደዚሁ ነው።

20ዕንጨት ከሌለ እሳት ይጠፋል፤

አሾክሻኪ ከሌለም ጠብ ይበርዳል።

21ከሰል ፍምን፣ ዕንጨትም እሳትን እንደሚያቀጣጥል፣

አዋኪ ሰውም ጠብን ያባብሳል።

22የሐሜተኛ ቃል እንደ ጣፋጭ ጕርሻ ነው፤

ወደ ሰው ውስጠኛው ክፍል ዘልቆ ይገባል።

23ክፋትን በልብ ቋጥሮ ለስላሳ ቃል የሚናገር ከንፈር፣

በብር ፈሳሽ26፥23 ወይም በሚያብለጨልጭ ነገር እንደ ተለበጠ የሸክላ ዕቃ ነው።

24ተንኰለኛ በከንፈሩ ይሸነግላል፤

በልቡ ግን ክፋትን ይቋጥራል።

25ንግግሩ ማራኪ ቢሆንም አትመነው፤

ሰባት ርኩሰት ልቡን ሞልቶታልና።

26ተንኰሉ በሽንገላው ይሸፈን ይሆናል፤

ነገር ግን ክፋቱ በጉባኤ ይገለጣል።

27ጕድጓድ የሚምስ ራሱ ይገባበታል፤

ድንጋይ የሚያንከባልልም ተመልሶ በላዩ ላይ ይገለበጥበታል።

28ሐሰተኛ ምላስ የጐዳቻቸውን ትጠላለች፤

ሸንጋይ አንደበትም ጥፋትን ታመጣለች።