ማሕልየ መሓልይ 1 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

ማሕልየ መሓልይ 1:1-17

1ከመዝሙር ሁሉ የሚበልጥ የሰሎሞን መዝሙር።

ሙሽራዪቱ

2በከንፈሩ መሳም ይሳመኝ

ፍቅርህ ከወይን ጠጅ ይልቅ ደስ ያሰኛልና።

3የሽቱህ መዐዛ ደስ ያሰኛል፤

ስምህ እንደሚፈስስ ሽቱ ነው፤

ታዲያ ቈነጃጅት ቢወድዱህ ምን ያስደንቃል!

4ይዘኸኝ ሂድ፤ እንፍጠን፤

ንጉሡ ወደ ዕልፍኞቹ አምጥቶኛል።

ባልንጀሮቿ

በአንተ1፥4 በዕብራይስጥ ነጠላ ተባዕታይ ነው። ደስ ይለናል፤ ሐሤትም እናደርጋለን፤

ከወይን ጠጅ ይልቅ ፍቅርህን እንወድሳለን።

ሙሽራዪቱ

አንተን እንደዚህ ማፍቀራቸው ትክክል ነው።

5እናንት የኢየሩሳሌም ቈነጃጅት ሆይ፤

እኔ ጥቍር ነኝ፤ ይሁን እንጂ ውብ ነኝ፤

ጥቍረቴ እንደ ቄዳር ድንኳኖች፣

እንደ ሰሎሞን1፥5 ወይም ሳልማ ቤተ መንግሥት መጋረጃዎችም ነው።

6ጥቍር ስለሆንሁ ትኵር ብላችሁ አትዩኝ፤

መልኬን ያጠቈረው ፀሓይ ነውና፤

የእናቴ ልጆች ወንድሞቼ ተቈጡኝ፤

የወይን ተክል ቦታዎችም ጠባቂ አደረጉኝ፤

የራሴን የወይን ተክል ቦታ ተውሁት።

7ውዴ ሆይ፤ መንጋህን የት እንደምታሰማራ፣

በቀትርም የት እንደምትመስጋቸው

እባክህ ንገረኝ፤

በወዳጆችህ መንጎች ኋላ፣

ፊቷን ሸፍና እንደምትቅበዘበዝ ሴት ለምን ልሁን?

ባልንጀሮቿ

8አንቺ ከሴቶች ሁሉ ይበልጥ የተዋብሽ ሆይ፤ የማታውቂ ከሆነ፣

የበጎቹን ዱካ ተከተዪ፤

የፍየል ግልገሎችሽንም፣

በእረኞቹ ድንኳን አጠገብ አሰማሪ።

ሙሽራው

9ውዴ ሆይ፤ የፈርዖንን ሠረገሎች ከሚስቡ ፈረሶች መካከል፣

በአንዲቱ ባዝራ መሰልሁሽ።

10ጕንጮችሽ በጕትቻ፣

ዐንገትሽም በዕንቍ ሐብል አጊጠዋል።

11እኛም ባለ ብር ፈርጥ፣

የወርቅ ጕትቻ እናሠራልሻለን።

ሙሽራዪቱ

12ንጉሡ ማእዱ ላይ ሳለ፣

ሽቱዬ መዐዛውን ናኘው።

13ውዴ ለእኔ በጡቶቼ መካከል እንዳረፈ፣

በመቋጠሪያ እንዳለ ከርቤ ነው።

14ውዴ ለእኔ ከዓይንጋዲ የወይን ተክል ቦታ

እንደ መጣ የሄና አበባ ዕቅፍ ነው።

ሙሽራው

15ውዴ ሆይ፤ እንዴት ውብ ነሽ!

እንዴትስ ያለሽ ቈንጆ ነሽ!

ዐይኖችሽም እንደ ርግብ ዐይኖች ናቸው።

ሙሽራዪቱ

16አንተ ውዴ ሆይ፤ እንዴት ውብ ነህ!

እንዴትስ ታምራለህ!

ዐልጋችንም እንደ ለምለም ሣር ነው።

ሙሽራው

17የቤታችን ተሸካሚዎች ዝግባዎች፣

የጣራችን ማዋቀሪያዎችም ጥዶች ናቸው።