ሆሴዕ 9 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

ሆሴዕ 9:1-17

በእስራኤል ላይ የሚደርሰው ቅጣት

1እስራኤል ሆይ፤ ደስ አይበልሽ፤

እንደ ሌሎችም ሕዝቦች ሐሤት አታድርጊ፤

ለአምላክሽ ታማኝ አልሆንሽምና፤

በየእህል ዐውድማውም ላይ፣

ለጋለሞታ የሚከፈለውን ዋጋ ወድደሻል።

2የእህል ዐውድማዎችና የወይን መጭመቂያዎች ሕዝቡን አይመግቡም፤

አዲሱም የወይን ጠጅ ይጐድልባቸዋል።

3በእግዚአብሔር ምድር አይቀመጡም፤

ኤፍሬም ወደ ግብፅ ይመለሳል፤

የረከሰውንም ምግብ9፥3 በሥርዐቱ መሠረት ያልነጻ ማለት ነው በአሦር ይበላል።

4የወይን ጠጅን ቍርባን ለእግዚአብሔር አያፈስሱም፤

መሥዋዕታቸውም ደስ አያሰኘውም፤

እንዲህ ዐይነቱ መሥዋዕት ለእነርሱ የሐዘንተኞች እንጀራ ይሆንባቸዋል፤

የሚበሉትም ሁሉ ይረክሳሉ።

ይህ ምግብ ለገዛ ራሳቸው ይሆናል፤

ወደ እግዚአብሔርም ቤተ መቅደስ አይገባም።

5በእግዚአብሔር የበዓል ቀናት፣

በዓመት በዓሎቻችሁም ቀን ምን ታደርጋላችሁ?

6ከጥፋት ቢያመልጡም እንኳ፣

ግብፅ ትሰበስባቸዋለች፤

ሜምፎስም ትቀብራቸዋለች።

የብር ሀብታቸውን ዳዋ ያለብሰዋል፤

ድንኳኖቻቸውንም እሾኽ ይወርሳቸዋል።

7የቅጣት ቀን መጥቷል፤

የፍርድም ቀን ቀርቧል፤

እስራኤልም ይህን ይወቅ!

ኀጢአታችሁ ብዙ፣

ጠላትነታችሁም ታላቅ ስለሆነ፣

ነቢዩ እንደ ሞኝ፣

መንፈሳዊውም ሰው እንደ እብድ ተቈጥሯል።

8ነቢዩ ከአምላኬ ጋር ሆኖ፣

የኤፍሬም ጠባቂ ነው፤9፥8 ወይም ነቢዩ የኤፍሬም ጠባቂ ነው፤ የአምላኬ ሕዝብ…

ዳሩ ግን በመንገዱ ሁሉ ወጥመድ፣

በአምላኩም ቤት ጠላትነት ይጠብቀዋል።

9በጊብዓ እንደ ነበረው፣

በርኩሰት ውስጥ ተዘፍቀዋል፤

እግዚአብሔር ክፋታቸውን ያስባል፤

ስለ ኀጢአታቸውም ይቀጣቸዋል።

10“እስራኤልን ማግኘቴ፣

የወይንን ፍሬ በምድረ በዳ የማግኘት ያህል ነበር፤

አባቶቻችሁንም ማየቴ፣

የመጀመሪያውን የበለስ ፍሬ የማየት ያህል ነበር፤

ወደ ብዔልፌጎር በመጡ ጊዜ ግን፣

ለዚያ አሳፋሪ ጣዖት ራሳቸውን ለዩ፤

እንደ ወደዱትም ጣዖት የረከሱ ሆኑ።

11የኤፍሬም ክብር እንደ ወፍ በርሮ ይጠፋል፤

መውለድ፣ ማርገዝና መፅነስ የለም።

12ልጆችን ቢያሳድጉ እንኳ፣

ልጅ አልባ እስኪሆኑ ድረስ እነጥቃቸዋለሁ፤

ፊቴን ከእነርሱ በመለስሁ ጊዜ፣

ወዮ ለእነርሱ!

13ኤፍሬምን እንደ ጢሮስ፣

በመልካም ስፍራ ተተክሎ አየሁት፤

አሁን ግን ኤፍሬም ልጆቹን፣

ለነፍሰ ገዳዮች አሳልፎ ይሰጣል።”

14እግዚአብሔር ሆይ፤ ስጣቸው፤

ምን ትሰጣቸዋለህ?

የሚጨነግፉ ማሕፀኖችን፣

የደረቁ ጡቶችን ስጣቸው።

15“በጌልገላ ካደረጉት ክፋታቸው ሁሉ የተነሣ፣

እኔ በዚያ ጠላኋቸው፤

ስለ ሠሩት ኀጢአት፣

ከቤቴ አሳድዳቸዋለሁ፤

ከእንግዲህም አልወድዳቸውም፤

መሪዎቻቸው ሁሉ ዐመፀኞች ናቸው።

16ኤፍሬም ተመታ፤

ሥራቸው ደረቀ፤

ፍሬም አያፈሩም፤

ልጆች ቢወልዱም እንኳ፣

ተንከባክበው ያሳደጓቸውን ልጆቻቸውን እገድላለሁ።”

17ባለመታዘዛቸው ምክንያት፣

አምላኬ ይጥላቸዋል፤

በአሕዛብም መካከል ተንከራታች ይሆናሉ።