መዝሙር 34:11-22 NASV

መዝሙር 34:11-22

ልጆቼ ሆይ፣ ኑ፤ ስሙኝ፤

እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ።

ሕይወትን የሚወድድ፣

በጎውንም ያይ ዘንድ ዕድሜን የሚመኝ ማን ነው?

አንደበትህን ከክፉ ነገር ከልክል፤

ከንፈርህንም ከሽንገላ ጠብቅ።

ከክፉ ሽሽ፤ መልካሙንም አድርግ፤

ሰላምን ፈልጋት፤ ተከተላትም።

የእግዚአብሔር ዐይኖች ወደ ጻድቃን ናቸው፤

ጆሮዎቹም ለጩኸታቸው ክፍት ናቸው።

መታሰቢያቸውን ከምድር ለማጥፋት፣

የእግዚአብሔር ፊት በክፉ አድራጊዎች ላይ ነው።

ጻድቃን ሲጮኹ፣ እግዚአብሔር ይሰማቸዋል፤

ከመከራቸውም ሁሉ ያድናቸዋል።

እግዚአብሔር ልባቸው ለተሰበረ ቅርብ ነው፤

መንፈሳቸው የተሰበረውንም ያድናቸዋል።

የጻድቅ መከራው ብዙ ነው፤

እግዚአብሔር ግን ከሁሉም ያድነዋል።

ዐጥንቶቹን ሁሉ ይጠብቃል፤

ከእነርሱም አንድ አይሰበርም።

ኀጢአተኞችን ክፋት ይገድላቸዋል፤

ጻድቃንን የሚጠሉ ይፈረድባቸዋል።

እግዚአብሔር የባሪያዎቹን ነፍስ ይቤዣል፤

እርሱንም መጠጊያ ያደረገ አይፈረድበትም።

Read More of መዝሙር 34