ኢዮብ 2 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

ኢዮብ 2:1-13

ሁለተኛው የኢዮብ ፈተና

1በሌላ ቀን ደግሞ፤ መላእክት2፥1 የዕብራይስጡ የእግዚአብሔር ልጆች ይላል። በእግዚአብሔር ፊት ለመቆም መጡ። ሰይጣንም ከእነርሱ ጋር በእግዚአብሔር ፊት ሊቆም መጣ። 2እግዚአብሔር ሰይጣንን፣ “ከወዴት መጣህ?” አለው።

ሰይጣንም፣ “በምድር ሁሉ ዞርሁ፤ ወዲያና ወዲህም ተመላለስሁባት” ብሎ ለእግዚአብሔር መለሰ።

3እግዚአብሔርም ሰይጣንን፣ “አገልጋዬን ኢዮብን ተመለከትኸውን? በምድር ላይ እንደ እርሱ ነቀፋ የሌለበት፣ ቅን፣ እግዚአብሔርን የሚፈራና ከክፋት የራቀ ሰው የለም፤ ያለ ምክንያት እንዳጠፋው ብትወተውተኝም፣ ይኸው ፍጹምነቱን እንደ ጠበቀ ነው” አለው።

4ሰይጣንም እንዲህ ሲል መለሰ፤ “ ‘ቍርበት ስለ ቍርበት ነው’ እንዲሉ ሰው ለሕይወቱ ሲል ያለውን ሁሉ ይሰጣል፤ 5እስቲ እጅህን ዘርግተህ ዐጥንቱንና ሥጋውን ዳስስ፤ በርግጥ ፊት ለፊት ይሰድብሃል።”

6እግዚአብሔርም ሰይጣንን፣ “እነሆ፤ እርሱ በእጅህ ነው፤ ሕይወቱን ግን እንዳትነካ” አለው።

7ከዚህ በኋላ ሰይጣን ከእግዚአብሔር ፊት ወጥቶ ሄደ፤ ኢዮብንም ከእግር ጥፍሩ እስከ ራስ ጠጕሩ በክፉ ቍስል መታው። 8ኢዮብም ገላውን ለማከክ ገል ወሰደ፤ በዐመድም ላይ ተቀመጠ።

9ሚስቱም፣ “አሁንም ታማኝነትህን አልተውህምን? ይልቁን እግዚአብሔርን ርገምና ሙት!” አለችው።

10እርሱም፣ “አነጋገርሽ እንደማታስተውል2፥10 እንደማታስተውል ተብሎ የተተረጐመው የዕብራይስጥ ቃል፣ ግብረ ገባዊ ሕጸጽን ያመለክታል። ሴት ነው፤ መልካሙን ነገር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተቀበልን፤ ክፉውንስ አንቀበልምን? አላት።”

በዚህ ሁሉ፣ ኢዮብ በንግግሩ አልበደለም።

ሦስቱ የኢዮብ ወዳጆች

11ሦስቱ የኢዮብ ወዳጆች ቴማናዊው ኤልፋዝ፣ ሹሐዊው በልዳዶስ፣ ናዕማታዊውም ሶፋር በኢዮብ ላይ የደረሰውን መከራ ሁሉ በሰሙ ጊዜ፣ ሄደው ሊያስተዛዝኑትና ሊያጽናኑት በመስማማት ከየመኖሪያቸው በአንድነት መጡ። 12እነርሱም ከሩቅ ሆነው ሲመለከቱት እርሱ መሆኑን ሊለዩ አልቻሉም፤ በዚህ ጊዜ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ፤ ልብሳቸውንም ቀድደው በራሳቸው ላይ ትቢያ ነሰነሱ። 13ሰባት ቀንና ሰባት ሌሊት ከእርሱ ጋር መሬት ላይ ተቀመጡ፤ ሥቃዩ ታላቅ መሆኑንም ስለ ተረዱ፣ አንዳች ቃል የተናገረው አልነበረም።