መዝሙር 71 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

መዝሙር 71:1-24

መዝሙር 71

የሽማግሌ ጸሎት

71፥1-3 ተጓ ምብ – መዝ 31፥1-4

1እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተን መጠጊያ አደረግሁ፤

ከቶም አልፈር።

2በጽድቅህ ታደገኝ፤ አስጥለኝም፤

ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል፤ አድነኝም።

3ምንጊዜም የምሸሽበት፣

መጠጊያ ዐለት ሁነኝ፤

አንተ ዐለቴ ምሽጌ ነህና፣

ታድነኝ ዘንድ ትእዛዝህ ይውጣ።

4አምላኬ ሆይ፤ ከክፉ እጅ፣

ከግፈኛና ከጨካኝ መዳፍ አውጣኝ።

5ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ ተስፋዬ፣

ከልጅነቴም ጀምሮ መታመኛዬ ነህና።

6ከተወለድሁ ጀምሮ በአንተ ተደገፍሁ፤

ከእናቴ ማሕፀን ያወጣኸኝ አንተ ነህ፤

አንተ የዘወትር ምስጋናዬ ነህ።

7ብዙዎች እንደ ጕድ አዩኝ፤

አንተ ግን ጽኑ ዐምባዬ ነህ።

8ቀኑን ሙሉ ክብርህን ያወራ ዘንድ፣

አፌ በምስጋናህ ተሞልቷል።

9በእርጅናዬ ዘመን አትጣለኝ፤

ጕልበቴም ባለቀበት ጊዜ አትተወኝ።

10ጠላቶቼ ተነጋግረውብኛልና፣

ሕይወቴን ለማጥፋት የሚሹ በአንድ ላይ አሢረዋል፤

11እነርሱም፣ “እግዚአብሔር ትቶታል፤

የሚያስጥለው የለምና፣ ተከታትላችሁ ያዙት” አሉ።

12አምላክ ሆይ፤ ከእኔ አትራቅ፤

አምላኬ ሆይ፤ እኔን ለመርዳት ፍጠን።

13ባላንጣ የሆኑብኝ ይፈሩ፤ ይጥፉም፤

ሊጐዱኝ የሚፈልጉ፣

ንቀትንና ውርደትን ይከናነቡ።

14እኔ ግን ሁልጊዜ ተስፋ አደርጋለሁ፤

በምስጋና ላይ ምስጋና አቀርብልሃለሁ።

15አንደበቴ ስለ ጽድቅህ፣

ቀኑን ሙሉ ስለ ማዳንህ ይናገራል፤

ማቆሚያ ልኩንም አላውቅም።

16መጥቼ የጌታ እግዚአብሔርን ብርቱ ሥራ ዐውጃለሁ፤

የአንተን ጽድቅ ብቻ እናገራለሁ።

17አምላክ ሆይ፤ አንተ ከልጅነቴ ጀምረህ አስተማርኸኝ፤

እኔም እስከ ዛሬ ድረስ ድንቅ ሥራህን ዐውጃለሁ።

18አምላክ ሆይ፤ ሳረጅና ስሸብትም አትተወኝ፤

ክንድህን ለመጭው ትውልድ፣

ኀይልህን ኋላ ለሚነሣ ሕዝብ ሁሉ፣

እስከምገልጽ ድረስ።

19አምላክ ሆይ፤ ጽድቅህ እስከ ሰማያት ይደርሳል፤

አንተ ታላላቅ ነገሮችን አድርገሃል፤

አምላክ ሆይ፤ እንደ አንተ ያለ ማን ነው?

20ብዙ መከራና ጭንቅ ብታሳየኝም፣

ሕይወቴን እንደ ገና ታድሳለህ፤

ከምድር ጥልቅም፣

እንደ ገና ታወጣኛለህ።

21ክብሬን ትጨምራለህ፤

ተመልሰህም ታጽናናኛለህ።

22አምላኬ ሆይ፤ ስለ ታማኝነትህ፣

በበገና አመሰግንሃለሁ፤

የእስራኤል ቅዱስ ሆይ፤

በመሰንቆ እዘምርልሃለሁ።

23ዝማሬ በማቀርብልህ ጊዜ ከንፈሮቼ በደስታ ይሞላሉ፤

አንተ የተቤዠሃትም ነፍሴ እልል ትላለች።

24አንደበቴ ስለ ጽድቅህ፣

ቀኑን ሙሉ ያወራል፤

የእኔን መጐዳት የሚፈልጉ፣

ዐፍረዋልና፤ ተዋርደዋልም።