መዝሙር 128 – New Amharic Standard Version NASV

New Amharic Standard Version

መዝሙር 128:1-6

መዝሙር 128

የጻድቃን በረከት

መዝሙረ መዓርግ።

1እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሁሉ፣

በመንገዱም የሚሄዱ የተባረኩ ናቸው።

2የድካምህን ፍሬ ትበላለህ፤

ትባረካለህ፤ ይሳካልሃልም።

3ሚስትህ በቤትህ፣

እንደሚያፈራ ወይን ናት፤

ወንዶች ልጆችህ በማእድህ ዙሪያ፣

እንደ ወይራ ተክል ናቸው።

4እነሆ፤ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው፣

እንዲህ ይባረካል።

5እግዚአብሔር ከጽዮን ይባርክህ፤

በሕይወትህ ዘመን ሁሉ፣ የኢየሩሳሌምን ብልጽግና ያሳይህ፤

6የልጅ ልጅ ለማየትም ያብቃህ።

በእስራኤል ላይ ሰላም ይውረድ።