መዝሙር 123
የተጨነቀ ሰው ጸሎት
መዝሙረ መዓርግ።
1በሰማይ ዙፋን ላይ የተቀመጥህ ሆይ፤
ዐይኖቼን ወደ አንተ አነሣለሁ።
2የባሪያዎች ዐይን ወደ ጌታቸው እጅ፣
የባሪያዪቱም ዐይን ወደ እመቤቷ እጅ እንደሚመለከት፣
ምሕረት እስከሚያደርግልን ድረስ፣
የእኛም ዐይኖች ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ይመለከታሉ።
3እግዚአብሔር ሆይ፤ ንቀት በዝቶብናልና፣
ማረን፤ እባክህ ማረን።
4ነፍሳችን የቅንጡዎች ስድብ፣
የትዕቢተኞችም ንቀት እጅግ በዝቶባታል።